የሁለት ዓመቱ ጦርነት ጋዛን ምን ያህል አወደማት?

በጦርነት የተጎዱ ሕንፃዎች እና ፍርስራሾች የሚያሳይ ጥቁር እና ነጭ ምሥል በጋዛ ካርታ ቅርጽ ውስጥ ሆኖ ከመካከል ላይ ከወደሙት ሕንጻዎች ፍርስራሹ ብቻውን የቆመ ንድፍ የሚያሳይ ምሥል። በግራ በኩል የሜዲትራኒያን ባሕር፣ የወደሙ ሕንጻዎች እና ቤቶች በደበዘዘ ሰማያዊ ቀለም ተሸፍነው ይታያሉ።

የሁለት ዓመቱ ጦርነት ጋዛን አውድሟታል።

እስራኤል በጋዛ ላይ ያካሄደችው መጠነ ሰፊ የቦምብ ድብደባ እና የእግረኛ ሠራዊት ጥቃት ከ67 ሺህ በላይ ፍልስጤማውያንን መግደሉን በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። የግዛቲቱ አጠቃላይ የሚሆነው ሕዝብ ከመኖሪያው እንዲለቅ ተገድዷል፤ የተባበሩት መንግሥታት እንደሚለው በጋዛ ውስጥ ካሉ ቤቶች አብዛኞቹ ወድመዋል ወይም ጉዳት ደርሶባቸዋል።

ይህ የእስራኤል ጥቃት የተጀመረው ሐማስ ባልታየ ሁኔታ ወደ እስራኤል ዘልቆ በመግባት በፈጸመው ጥቃት 1,200 ሰዎች ከተገደሉ እና 251 ሰዎች ታግተው ወደ ጋዛ ከተወሰዱ በኋላ ነው።

ከአውሮፓውያኑ 2007 አንስቶ ጋዛን የተቆጣጠረው እና እስራኤልን ማጥፋት ዓላማው ያደረገውን የሐማስን ወታደራዊ እና አስተዳደራዊ አቅምን መደምሰስ በጋዛ ላይ ያካሄደችው ወታደራዊ ዘመቻ ግብ መሆኑን እስራኤል ስትገልጽ ቆይታለች።

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንዳሉት የመጀመሪያው ዙር የጋዛ የሰላም ዕቅድ እስራኤል እና ሐማስ ጦርነቱን በዘላቂነት ለማስቆም፣ የእስራኤል ታጋቾች እና ፍልስጤማውያን እስረኞችን ለማስለቀቅ፣ የእስራኤል ኃይሎችን ከጋዛ ለማስወጣት እና ወደ ጋዛ እርዳታ እንዲገባ ያስችላል።

ጋዛ 41 ኪሎ ሜትር ርዝመት እና 10 ኪሎ ሜትር ስፋት ያላት ትንሽዬ ሰርጥ ስትሆን፣ በሦስት በኩል የሚያዋስኗት እስራኤል እና ግብፅ ጥብቅ ቁጥጥር የሚያደርጉበት የተዘጋ ድንበር አላት። በስተ ምዕራ�� ደግሞ ከሜዲትራኒያን ባሕር ጋር የምትዋሰን ቢሆንም የባሕር መስመሩ በእስራኤል ቁጥጥር የተዘጋ ነው። ጋዛ በውስጧ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ይኖርባታል።

ዩናይትድ ኪንግደምን፣ አውሮፓን፣ ሰሜን አፍሪካን እና ጋዛን የሚያሳይ ካርታ

ከ90% በላይ የሚሆኑት የጋዛ ሕንጻዎች ወድመዋል ወይም ጉዳት ደርሶባቸዋል ተብሎ ይገመታል፤ የጤና አገልግሎት፣ የውሃ አቅርቦት፣ የንጽህና እና የጽዳት ሥርዓቶች በጦርነቱ ወድመዋል፤ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባለሙያዎች እንዳሉት ጋዛ ከተማ ውስጥ ረሃብ ተከስቷል። የተባበሩት መንግሥታት አጣሪ ኮሚሽን እስራኤል ጋዛ ውስጥ በሚገኙ ፍልስጤማውያን ላይ የዘር ማጥፋት ፈጽማለች ያለ ሲሆን፣ እስራኤል ግን የኮሚሽኑን ሪፖርት “የተዛባ እና ሐሰተኛ” በማለት ውድቅ አድርጋዋለች። ይህ ሥዕላዊ መግለጫ እንሚያሳየው አብዛኞቹ የጋዛ ክፍሎች ለሰዎች መኖሪያነት ከመሆን ውጪ ሆነዋል።

ውድመቱ ምን ያህል ሰፊ ነው?

የእስራኤል ወታደራዊ ዘመቻ መጀመሪያ ላይ ትኩረት አድርጎ የነበረው የሐማስ ተዋጊዎች ከሰላማዊ ሰዎች መካከል ተደብቀውበታል በምትለው በሰሜናዊ ጋዛ ላይ ነበረ። ሐማስ ግን ይህንን ያስተባብላል።

በጥምቅት 12/2023 የተዘጋጀው የጋዛ ካርታ ውድመት የደረሰባቸውን ቦታዎች በቀይ ያሳያል። ጎላ ያለ ቀይ ቀለም የሚታይበት በስተ ሰሜን ከእስራኤል ጋር የሚዋሰናውን ቤት ሃኑንን ያመለክታል። ትናንሽ ቀይ ነጥቦች ደግሞ በጋዛ ከተማ ውስጥ የሚታዩ ሲሆን፣ ሰሜናዊ ጋዛ በደቡባዊ ክፍሉ ላይ ትንሽ ነጥቦች ይታዩበታል።

ከእስራኤል ድንበር በሁለት ኪሜ ብቻ የምትርቀው ሰሜናዊቷ ከተማ ቤት ሃኑን በእስራኤል ጥቃት በመጀመሪያ ላይ ከተመቱት አካባቢዎች አንዷ ናት። በዚህም ከተማዋ ከባደ ጉዳት ደርሶባታል።

በኅዳር 29/2023 የተዘጋጀው ካርታ በጋዛ ከተማ ውስጥ እና በሰሜናዊ ጋዛ የደረሰውን ውድመት በቀይ ያሳያል። ውድመቱ ወደ ደቡብም ተስፋፍቷል። ግዛቲቱን አቋርጦ የሚያልፈው የዋዲ ጋዛ ወንዝ ይታያል።

እስራኤል ጋዛ ከተማን እና ሌሎች ሰሜናዊ የከተማ ማዕከላትን በቦምብ መደብደቧን ቀጥላ፣ በጥቅምት 2023 ማብቂያ ላይ የእግረኛ ሠራዊት ጥቃት ከመጀመሯ በፊት ነዋሪዎች ከዋዲ ጋዛ ወንዝ በስተደቡብ እንዲሄዱ አዝዛለች።

ነገር ግን በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የጋዛ ነዋሪዎች ከሰሜን ወደ ደቡብ እየሸሹ በነበረበት ጊዜ በደቡብ ጋዛ በሚገኙ ከተሞች ላይ እስራኤል የአየር ጥቃት እየፈጸመች ነበረ። በኅዳር መጨረሻ ላይ የግዛቲቱ ደቡባዊ ክፍሎች በሰሜን እንደሆነው ሁሉ ወደ ፍርስራሽነት ተቀይረዋል

በጥር 29/2024 የወጣው ካርታ በደቡባዊ ጋዛ የሚገኘውን ኻን ዩኒስን ያሳያል፣ ውድመቱን ለማመልከት በቀይ ተሸፍኗል። ጋዛ ከተማ እና መካከለኛው ጋዛም የበለጠ ከባድ ውድመት ደርሶባቸዋል።

በታኅሣሥ ወር መጀመሪያ ላይ እስራኤል በደቡባዊ እና በመካከለኛው ጋዛ ላይ ስታካሂድ የነበረው የቦምብ ጥቃት ስታጠናክር፤ ከዚያም በኻን ዩኒስ ላይ የእግረኛ ሠራዊት ጥቃት ከፍታለች። በጥር 2024 በጋዛ ከሚገኙት ሕንፃዎች ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ጉዳት ደርሶባቸዋል ወይም ወድመዋል።

ጥር 11/2025 የተዘጋጀው ካርታ አሁን ሙሉ በሙሉ ቀይ የሆነውን የጋዛ ከተማን ያሳያል።

በጥር 2025 የተኩስ አቁም በታወጀበት ጊዜ በጋዛ ከተማ ከፍተኛ ውድመት ያጋጠመ ሲሆን፣ በጋዛ ሰርጥ ውስጥ ከነበሩት ሕንጻዎች ወደ 60% የሚጠጉት ጉዳት ደርሶባቸው ነበር። የጋዛ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በወቅቱ እንዳሳወቀው ከ46 ሺህ በላይ ፍልስጤማውያን ተገድለዋል።

በነሐሴ 19/2025 የተዘጋጀው ካርታ ጉዳቱ አስከፊ የሆነበትን የደቡባዊ ራፋህ ክፍልን ያሳያል።

እስራኤል በመጋቢት ወር ከተኩስ አቁም ስምምነቱ ከወጣች በኋላ በደቡባዊ ራፋህ ያሉ አካባቢዎችን ጨምሮ ውድመቱ ቀጥሏል። የተባበሩት መንግሥታት እንደገለጸው በጋዛ ውስጥ ከ90% በላይ የሚሆኑት የመኖሪያ ቤቶች በጦርነቱ ወቅት ጉዳት ደርሶባቸዋል።

በጦርነቱ ወቅት በእስራኤል፣ በዩናይትድ ኪንግደም እና በበርካታ ምዕራባውያን አገራት በሽብር ቡድንነት የተፈረጀው ሐማስ እና ደጋፊዎቹ የሆኑ ሌሎች ታጣቂ ቡድኖች ከእስራኤል ኃይሎች ጋር ከባድ የእግረኛ ውጊያ አካሂደዋል። በተለይ በጦርነቱ የመጀመሪያ ወራት በሺዎች የሚቆጠሩ ሮኬቶችን ወደ እስራኤል ተኩሰዋል። በጦርነቱ የጋዛ ሁሉም ክፍሎች ውስጥ የሚገኙ ተቋማት ወደ ፍርስራሽነት ተቀይረዋል። ሆስፒታል እና መስጂዶች ሲፈርሱ፣ የእርሻ ልማት ቦታዎች በ���ስራኤል ወታደሮች ከባድ ተሽከርካሪዎች እና ታንኮች እንዲወድሙ ተደርገዋል። ሐማስ ሆስፒታልን የመሳሰሉ ሰላማዊ ተቋማትን ለወታደራዊ ዓላማው ይጠቀምባቸዋል በማለት እስራኤል የምትከስስ ሲሆን፣ ሐማስ ግን ይህንን ያስተባብላል።

ከሰኔ 2023 እስከ መስከረም 2025 የተደረጉ ለውጦችን የሚያሳይ የጋዛ ሰርጥ ንጽጽራዊ የሳተላይት ካርታ። የእርሻ ቦታዎች፣ ገበያዎች እና የመኖሪያ አካባቢዎች ውድመት፤ መፈናቀል፣ የራፋህ ድንበር መተላለፊያ መዘጋት እና አካባቢዎችን ወደ ጊዜያዊ መጠለያ ካምፖች መለወጥን ጨምሮ የጦርነት ጉዳት እና ሰብአዊ ተጽእኖውን የሚያሳዩ ገላጭ ፎቶዎች።

ከጦርነቱ በፊት ከ2.1 ሚሊዮኑ የጋዛ ሕዝብ አብዛኛው በራፋህ እና ኻን ዩኒስ በደቡብ፣ በዴር አል-ባላህ በማዕከላዊ እና ጋዛ ከተማ በተባሉት በአራት ዋነኛ ከተሞች ውስጥ ይኖሩ ነበረ። ሐማስ በእስራኤል ላይ ጥቃት ከፈጸመ በኋላ በነበሩት 10 ቀናት ውስጥ እስራኤል ባካሄደችው ጥቃት ወደ ግማሽ የሚጠጋው ነዋሪ መኖሪያውን ለቅቆ እንዲሄድ እንዳስገደደው የተባበሩት መንግሥታት የፍልስጤም ስደተኞች ድርጅት አመልክቷል።

የጋዛን አጠቃላይ ሕዝብ በግራጫ ቀለም እና በተወሰኑ ቀናት የተፈናቀለውን ደግሞ በሐምራዊ ቀለም የሚያሳይ ሥዕላዊ መረጃ። በእስራኤል ጥቃት የመጀመሪያ ቀን 123,538 ሰዎች ተፈናቅለዋል፣ በአምስት ቀናት ውስጥ ወደ 423,378 ከፍ ብሏል። በተጨማሪም እስራኤል በጥቅምት 13 ነዋሪዎች ከሰሜናዊ ጋዛ እንዲወጡ ካዘዘች ከሦስት ቀናት በኋላ 1 ሚሊዮን ሰዎች ተፈናቅለዋል።

ጦርነቱ ከተጀመረ ከ15 ወራት በኋላ የተኩስ አቁም ይፋ በሆነበት ወቅት ወደ 1.9 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎች በጋዛ ውስጥ የተፈናቀሉ ሲሆን፣ አሁንም ድረስ ወደ ቤታቸው መመለስ አልቻሉም።

በጥር 14/2024 የተዘጋጀው ሥዕላዊ መረጃ እንደሚያመለክተው 1,900,000 ሰዎች ተፈናቅለዋል፣ ይህም ከጋዛ ሕዝብ 90% ነው።

እስራኤል የወታደራዊ ዘመቻዋን ትኩረት ስትቀይር ነዋሪዎች ብዙ ጊዜ ወደ ተለያዩ ቦታዎች ተዛውረዋል፣ በመጀመሪያ በሰሜን የሚገኙ ሰዎች ከዋዲ ጋዛ ወንዝ በስተደቡብ እንዲሄዱ ስታዝዝ፣ ይህም ጋዛ ሰርጥን በግምት በግማሽ ይከፍላል፣ በኋላ ላይም ነዋሪዎች በደቡብ በተከታታይ “በመውጫ ቀጣናዎች” በኩል ለቅቀው እንዲወጡ ተደርገዋል።

https://ichef.bbci.co.uk/images/ic/raw/p0m5vbxg.jpg

የእስራኤል ጦር ሠራዊት በአካባቢው ዘመቻ ከማካሄዱ በፊት ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ የሚያስጠነቅቁ በራሪ ወረቀቶችን ይበትናል።ነገር ግን ከሁሉም የእስራኤል ጥቃቶች በፊት ተመሳሳይ ማስጠንቀቂያዎች አይሰጡም።

በመስከረም 16/2025 እስራኤል አዲስ የለቃችሁ ውጡ ትዕዛዝ ካወጣች በኋላ የተፈናቀሉ ፍልስጤማውያን ንብረታቸውን ይዘው በማዕከላዊ ጋዛ በሚገኘው ኑሴራት የስደተኞች ካምፕ መንገድ ላይ ወደ ደቡብ እያመሩ፤ ሰዎች ከባድ ንብረቶችን ከጫኑ ተሽከርካሪዎች አጠገብ ይራመዳሉ። በግራ በኩል የባሕር ዳርቻ፣ በቀኝ በኩል የተጎዱ ሕንፃዎች እና የተበታተኑ ፍርስራሾች ይታያሉ።
ጌቲ ኢሜጅስ
በነሐሴ ወር እስራኤል የጋዛ ከተማ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ አዲስ ትዕዛዝ ከሰጠች በኋላ በሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን እንደገና ለቅቀው እንዲወጡ ተገድደዋል።

ክልከላ የተጣለባቸው አካባቢዎች ጨመሩ

በመጋቢት 18/2025 የተዘጋጀ የጋዛ ሰርጥ ካርታ፣ ክልከላ እና ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ የታዘዙባቸው ቦታዎችን ያሳያል። ምልክት የተደረገባቸው ከተሞች ሰሜን ጋዛ፣ ጋዛ ከተማ፣ ዴር አል-ባላህ፣ ኻን ዩኒስ እና ራፋህን ያካትታሉ። ሐምራዊው ቀለም ከእስራኤል እና ከግብፅ ጋር በሚዋስነው ድንበር ላይ ክልከላዎች ወይም ለቅቀው እንዲወጡ የታዘዙባቸውን ቦታዎች ያሳያሉ።

እስራኤል የተኩስ አቁም ስምምነቱ አንዲያበቃ ካደረገች በኋላ ተጨማሪ የጋዛ አካባቢዎችን በመለየት መንቀሳቀስ የማይቻልባቸው ቀጠናዎች - በማድረግ ክልከላ አንዲጣለባቸው አድርጋለች ወይም አካባቢዎቹን በመለየት ነዋሪዎች ሙሉ ለሙሉ ለቅቀው እንዲወጡ የሚያደርግ ትዕዛዝ, ደርሷቸዋል። በመጀመሪያ ላይ አካባቢዎችን ለቅቆ የመውጣት ትዕዛዝ ሁለት ቦታዎችን የሚሸፍን ነበረ፤ እነሱም ሰሜን ጋዛ እና ኻን ዩኒስ አስተዳደሮች ውስጥ በድንበር አካባቢዎች ላይ የተ��ለ "የተከለከሉ" ቦታዎችን የሚጨምር ነው። የእርዳታ ድርጅቶች "በተከለከሉ" ቦታዎች ወስጥ ለመንቀሳቀስ ከእስራኤል ባለሥልጣናት ጋር መቀናጀት ይኖርባቸዋል። ሐማስ የእርዳታ አቀርቦቶችን እየተቆጣጠረ ነው በማለት እስራኤል ወደ ጋዛ የሚገባውን ሰብአዊ እርዳታ ከመጋቢት ወር ጀምራ አግዳለች። የእርዳታ ድርጅቶች በቂ አይደለም ቢሉም ውስን የእርዳታ አቅርቦት ብቻ ነበር የፈቀደችው።

በሚያዝያ መጀመሪያ ላይ በተባበሩት መንግሥታት የሚደገፉ ሁሉም ዳቦ ቤቶች ሲዘጉ፣ የአትክልት አቅርቦት በጣም ውስን ሆነ እንዲሁም ሆስፒታሎች የሚያቀርቧቸው መድኃኒት በጣም በመቀነሱ በኮታ ማዳረስ ጀመሩ። አክሽን ኤይድ የተባለው መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት በጋዛ ውስጥ “የረሃብ እና የውሃ ጥም” ቀውስ እያንዣበበ ነው ሲል አስጠንቅቆ ነበረ። ጦርነቱ ቢያበቃ እንኳን እስራኤል ዜጎቿን ለመከላከል የሚያስችል ጋዛ ውስጥ የደኅንነት ቀጣና እንዲሚቋቋም የመከላከያ ሚኒስቴሯ በሚያዝያ 16 አስታውቀዋል። ሐማስ ግን ዘላዊ የተኩስ አቁም ከተደረሰ በኋላ የእስራኤል ኃይሎች ከጋዛ ለቅቀው መውጣት አለባቸው ሲል ጠይቋል። በወቅቱ 70 በመቶ የሚደርሰው የጋዛ ክፍል የእስራኤል ዕገዳ - የተጣለባቸው ሲሆን፣ ይህም አብዛኞቹን በሰሜን የሚገኙትን ሰሜን ጋዛ እና ጋዛ ከተማን ጨምሮ በስተደቡብ ደግሞ ሙሉውን የራፋህ አካባቢ እንደሚያካትት የተባበሩት መንግሥታት መረጃ ያመለክታል።

በሚያዝያ 15/2025 የተዘጋጀው የጋዛ ሰርጥ ካርታ በሐምራዊ ቀለም የተከለከሉ እና ለቆ በመውጣት ትዕዛዝ ስር ያሉ ቦታዎችን ያሳያል። መለያዎቹ በአብዛኛው ትዕዛዙ የሚመለከታቸውን የሰሜን ጋዛ አካባቢዎች፣ ጋዛ ከተማ እና ሙሉ በሙሉ የሚመለከተውን በደቡብ የሚገኘውን ራፋህ ያሳያሉ።

በግንቦት ወር እስራኤል ‘የጌዲዮን ሰረገላ’ የሚል ስያሜ የሰጠችውን የእግረኛ ሠራዊት ዘመቻ ማካሄድ ጀመረች። ይህ ጥቃት ዓላማ ያደረገው ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ሟቾች የሚገኙባቸውን ቀሪ 48 ታጋቾችን ማስለቀቅ እና የፍልስጤሙን ታጣቂ ቡድን የሐማስን “ሽንፈት ማጠናቀቅ” መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ተናግረው ነበር። ከዚያ ጊዜ አንስቶ አካባቢው በእስራኤል ለቅቆ የመውጣት ትዕዛዝ እና ሌሎች ዕገዳዎች ስር ቆይቷል። ይህም ከጋዛ አጠቃላይ ይዞታን 82% የሚሸፍን መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት መረጃ ያሳያል። የዘመቻው የመጀመሪያ ምዕራፍ ትኩረት ያደረገው በራፋህ፣ በኻን ዩኒስ እና በሰሜናዊ ጋዛ ውስጥ በሚገኙ ዒላማዎች ላይ ሲሆን፣ በነሐሴ ወር ላይ እስራኤል የሐማስ “ጠንካራ ይዞታ” የምትላትን ጋዛን ሙሉ በመውረር ለመቆጣጠር ያላትን ዕቅድ ይፋ አደረገች።

ጋዛ ከተማ ከጦርነቱ በፊት 775 ሺህ ሕዝብ የሚኖርባት ሕዝብ በተጨናነቀ ሁኔታ የሚገኝባት የጋዛ ሰርጥ ክፍል ነበረች።

በጥቅምት 1/2025 የወጣው የጋዛ ሰርጥ ካርታ በክልከላ እና ለቆ በመውጣት ትዕዛዝ ስር ያሉ አካባቢዎችን በሐምራዊ ቀለም ያሳያል። መላው የሰሜን ጋዛ እና የጋዛ ከተማ አካባቢዎች ከሞላ ጎደል ከሁሉም የራፋህ እና የኻን ዩኒስ እንዲሁም የዴር አል-ባላህ ምዕራባዊ ክፍሎች ጋር ተካትተዋል። በጋዛ ደቡብ ምሥራቅ የሚገኘው አል-ማዋሲ በእስራኤል በተጣሉ ገደቦች ስር ያልሆነ ጠባብ ነው።

እዚያ የነበሩ ሰዎች የአየር ጥቃት ወደ ቀጠለበት እና የተባበሩት መንግሥታት አካባቢው የተጨናነቀ እና ለደኅንነት አስተማማኝ አይደለም ወዳለው እንዲሁም እስራኤል 'ሰብአዊ ቀጠና' ብላ ወደ ሰየመችው በሰርጡ ደቡብ ምዕራብ ወደሚገኘው አል-ማዋሲ እንዲሄዱ ታዝዘዋል። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች ለቀው በወጡባት ጋዛ ከተማ ረሃብ መከሰቱን በተባበሩት መንግሥታት የሚደገፈው አካል ነሐሴ 2025 ላይ አረጋግጧል። ቢሆንም ግን የጤና እና ሌሎች መሠረታዊ አገልግሎቶች በፈራረሱበት ሁኔታ ሌሎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የከተማዋ ነዋሪዎች አሁንም በአስከፊ ሰብአዊ ችግር ውስጥ እዚያው ይገኛሉ።

በጥቅምት 10/2025 የወጣ የጋዛ ሰርጥ ካርታ የእስራኤል ጦር የሰላም ስምምነቱ አካል ሆኖ መጀመሪያ ላይ ለመውጣት የተስማማበትን አካባቢ ያሳያል። አብዛኛውን ራፋህ እና ኻን ዩኒስን ጨምሮ በጋዛ ውስጥ ሰፊ የመከላከያ ቀጣና ይመሠርታል።

በጥቅምት ወር የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለ 20 ነጥብ የጋዛ የሰላም ዕቅዳቸውን ካስተዋወቁ በኋላ በድርድሩ ውጤት የታየ ሲሆን፣ እስራኤል እና ሐማስ የመጀመሪያ ምዕራፍ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ በመድረስ ታጋቾችን በመልቀቅ ጦርነቱ እንዲያበቃ መንገድ ከፍቷል። የእስራኤል ኃይሎች ለቅቀው በመውጣት ወደ ጋዛ ሰርጥ ዳርቻዎች ለመሄድ የተስማሙ ሲሆን፣ ይህም የጋዛ ሰርጥን 53% በቁጥጥራቸው ስር እንዲሆን ያደርጋል።

ጥቅምት 13/2025 በሐማስ ተይዘው የነበሩ 20 ታጋቾች ተለቀቁ። በምላሹ እስራኤል ውስጥ የታሰሩ ወደ 2 ሺህ የሚጠጉ ፍልስጤማውያን እስረኞች ተፈትተዋል። በስምምነቱ መሠረት ለሕዝቡ የሚያስፈልገውን አስቸኳይ እርዳታ የጫኑ መኪኖች ወደ ጋዛ እንዲገቡ ይፈቀድላቸዋል።

የመረጃ እና የምሥል ምንጮች

የውድመት ትንተናው ኮፐርኒከስ ሴንቲኔል-1 መረጃ በኮሪይ ሼር ከከኒ ግራጅዌት ሴንተር እና ጃሞን ቫን ደን ሆክ ከኦሪገን ስቴት ዩኒቨርስቲ። የካርታ መረጃ ከኦፕንስትሪትማፕ። የሕዝብ መፈናቀል መረጃ ከተባበሩት መንግሥታት። ለእንቅስቃሴ የተከለከሉ እና የተፈናቃይ ቀጣናዎች መረጃ ከኦቻ። የሳተላይት ምሥሎች ከፕላኔት ላብ ፒኤልሲ፣ ሌሎች ምሥሎች ከጌቲ እና ከሮይተርስ።