ሳን ፍራንሲስኮ በተቀነባበሩ ምርቶች ምክንያት ኮካ ኮላን ጨምሮ ግዙፍ የምግብ ኩባንያዎችን ከሰሰች

በካርቶን የታሸጉ ምግቦች

የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

የሳን ፍራንሲስኮ ከተማ ማክሰኞ ዕለት አስር ታዋቂ የምግብ አምራቾችን እጅግ በጣም በተቀነባበሩ ምርቶቻቸው ምክንያት ክስ መሠረተች።

ግዙፎቹ ኩባንያዎች ከከባድ በሽታዎች መጨመር ጋር የተያያዙ ምግቦችን ሆን ብለው እየሸጡ ነው ስትል ከስሳለች።

የከተማው ባለሥልጣናት የኩባንያዎቹ ዘዴዎች ከትምባሆ ኢንዱስትሪ ጋር ተመሳሳይ እንደሆኑ ይናገራሉ። የአካባቢ መንግሥታት የሕዝብ ጤና እንክብካቤ ወ��ዎችን መሸከም አለባቸው ብለው ይከራከራሉ።

ክራፍት ሄይንዝ፣ ሞንዴሌዝ እና ኮካ ኮላ ያሉ ድርጅቶች በካሊፎርኒያ ስለሸማቾች ጥበቃ እና ንግድ ውድድር የተመለከቱትን ሕጎች በመጣስ ሱስ የሚያስይዙ እና ጤናማ ያልሆኑ ምርቶችን ሆን ብለው ለገበያ አቅርበዋል ሲል ክሱ ገልጿል።

ክራፍት፣ ሞንዴሌዝ እና ሌሎች ተከሳሾች ተብለው የተሰየሙ ኩባንያዎች አስተያየት እንዲሰጡ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ወዲያውኑ ምላሽ አልሰጡም።

ምርቶቻቸው ኩኪሶች፣ ጣፋጮች እና ሌሎች በፋብሪካ የሚቀነባበሩ ምግቦችን ያካትታሉ።

"እነዚህ ኩባንያዎች የሕዝብ ጤና ቀውስ ፈጥረዋል፣ በጥሩ ሁኔታ ትርፍ አግኝተዋል፣ እና አሁን ላደረሱት ጉዳት ኃላፊነቱን መውሰድ አለባቸው" ሲሉ የሳን ፍራንሲስኮ ከተማ ዐቃቤ ሕግ ዴቪድ ቺዩ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል።

የኢንዱስትሪ ንግድ ቡድን በሆነው 'ኮንስዩመር ብራንድስ አሶስዬሽን' የምርት ፖሊሲ ከፍተኛ ምክትል ፕሬዝዳንት ሳራ ጋሎ እንዳሉት በከፍተኛ መጠን የተቀነባበሩ ምግቦች ላይ "ሳይንሳዊ ትርጓሜ" የለም ብለዋል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

"ምግቦች የተቀነባበሩ ስለሆኑ ብቻ የምግብን ሙሉ የንጥረ ነገር ይዘቱን ችላ በማለት ጎጂ አድርገው ለመመደብ መሞከር ሸማቾችን ያሳስታቸዋል እና የጤና ልዩነቶችን ያባብሳል" ሲሉ ሳራ ጋሎ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል።

የምግብ እና የመጠጥ አምራቾች ተጨማሪ ፕሮቲን እና ፋይበር፣ አነስተኛ ስኳር እና ሶዲየም እና ሰው ሰራሽ የቀለም ተጨማሪዎች የሌላቸውን አዳዲስ ምርቶችን እያስተዋወቁ ነው ሲሉ አክለዋል።

በሳን ፍራንሲስኮ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የቀረበው እና የመጀመሪያው የሆነው ይህ ክስ እጅግ በጣም የተቀነባበሩ ምግቦች ተደራሽነት እየጨመረ ከመጣው ከመጠን በላይ ውፍረት፣ የስኳር በሽታ፣ የልብ በሽታ፣ ካንሰር እና ሌሎች ሥር የሰደዱ በሽታዎች "በአስደናቂ ሁኔታ መጨመር" ጋር እንደሚገጣጠም ይከራከራል።

"ይህ ጉዳይ የተደበቁ የጤና ጉዳቶች ስላሏቸው የምግብ ምርቶች ነው" ሲል ክሱ ይገልጻል።

ከተማዋ ግዙፍ የምግብ ኩባንያዎች "አታላይ" የግብይት ስልቶቻቸውን እንዲቀይሩ የሚያስገድድ ትዕዛዝ እና የገንዘብ ቅጣት እንዲጣል ጠይቃለች።

እጅግ በጣም የተቀነባበሩ ምግቦች የደቀኑት ስጋት በአንዳንድ የግራ ዘመም ባለስልጣናት እና በትራምፕ አስተዳደር መካከል የጋራ መግባባት ላይ ደርሰዋል። ምንም እንኳን በጤና ሚኒስትር ሮበርት ኤፍ ኬኔዲ ጁኒየር ሌሎች አቋሞች፣ በክትባት ላይ ያላቸውን ጥርጣሬ ጨምሮ፣ አሁንም ድረስ አለመስማማት ቢኖርም።

በሚያዝያ ወር ኬኔዲ አሜሪካ ለምሳሌ ስምንት በተለምዶ ጥቅም ላይ የሚውሉ አርቲፊሻል የምግብ ቀለሞችን እንደምታግድ አስታውቀዋል።

የአሜሪካ የጤና ፀሐፊ እና አሜሪካን እንደገና ጤናማ እናድርጋት እንቅስቃሴ ኩባንያዎች እንደ የበቆሎ ሽሮፕ፣ የቅባት ዘሮች እና አርቲፊሻል ቀለሞች ያሉ ንጥረ ነገሮችን ከምርቶቻቸው እንዲያስወግዱ ጥሪ አቅርበዋል፤ ይህም ከጤና ችግሮች ጋር ያገናኛቸዋል።

ትራምፕ ወደ ዋይት ሀውስ ከተመለሱ በኋላ አንዳንድ የምግብ ኩባንያዎች በምርቶቻቸው ላይ ለውጦችን አስታውቀዋል። ኮካ ኮላ በዚህ ክረምት በአሜሪካ ውስጥ በሚሸጡት መጠጦች ውስጥ እውነተኛ የሸንኮራ አገዳ ስኳር ለመጠቀም ተስማምቷል።

የሳን ፍራንሲስኮ ክስ የምግብ ኩባንያዎች እጅግ በጣም የተቀነባበሩ ምግቦችን ሆን ብለው አስተዋውቀዋል በሚል በመንግስት አካል የቀረበ የመጀመሪያው ነው።

ነገር ግን በዚህ ዓመት በፔንስልቬንያ የሚገኙ አንድ ዳኛ እጅግ በጣም የተቀነባበሩ ምግቦች ለስኳር እና ለጉበት በሽታዎች እንዲጋለጥ አስተዋጽኦ አድርገዋል በሚል አንድ ግለሰብ ያቀረበውን ሌላ ክስ ውድቅ አድርገዋል።